በኢትዮጵያ ውስጥ አገልግሎቱን አቋርጦ የነበረው ዓለም አቀፉ የክሪፕቶ ከረንሲ መገበያያ መድረክ ባይናንስ (Binance)፣ አቋርጦት የነበረውን አገልግሎት በአገሪቱ ውስጥ በድጋሚ መጀመሩን ይፋ አደረገ። ኩባንያው ከኢትዮ ቴሌኮም ጋር በጋራ በመስራት አገልግሎቱን በድጋሚ መስጠት መጀመሩን አስታውቋል።
ባይናንስ አገልግሎቱን በድጋሚ ለመጀመር የቻለው፣ ከአገሪቱ የክሪፕቶ ከረንሲ ተቆጣጣሪ አካላት ጋር በጉዳዩ ላይ ሰፊ ውይይት ካደረገ በኋላ በደረሰበት ስምምነትና መግባባት መሰረት መሆኑን በገለጻው ላይ ጠቅሷል። ይህ ውሳኔ በኢትዮጵያ ውስጥ ዲጂታል የገንዘብ ግብይትን ለሚጠቀሙ ዜጎች አዲስ በር የሚከፍት ሆኗል።
ከዚህ ቀደም የኢትዮጵያ መንግስት የአገሪቱን ገንዘብ (ብር) ከክሪፕቶ ከረንሲ ያልተማከለ ግብይት ለመለየትና ለመጠበቅ የሚያስችሉ ጠንካራ የሕግና የቁጥጥር እርምጃዎችን መውሰድ መጀመሩ ይታወሳል።
ይህንን የመንግስትን አቋምና እርምጃ ተከትሎ፣ ባይናንስ እና የቴሌግራም ዋሌትን (Telegram Wallet) የመሰሉ ዓለም አቀፍ የክሪፕቶ መገበያያ መድረኮች በኢትዮጵያ ውስጥ የሚሰጡትን ስራ ማቋረጣቸውን ዋዜማ ቀደም ሲል መዘገቧ ይታወሳል። አሁን ግን አዳዲስ መመሪያዎችን በማክበር ስራው በይፋ ተጀምሯል።