በኬንያ የፖለቲካ ታሪክ ውስጥ አሳሳቢ የነበረውና የ«ጉኒዝም» (Goonism) ወይም የወሮበላነት ፖለቲካ በመባል የሚታወቀው ተግባር፣ በአሁኑ ወቅት በተደራጀ ስውር ኢኮኖሚ መልክ ተዋቅሮ ዳግም ማንሰራራቱ ተገለጠ። ከዚህ ቀደም የቀድሞው ፕሬዚዳንት ዳንኤል አራፕ ሞይ በስልጣን ላይ በነበሩበት ወቅት ይስተዋል የነበረው ይህ የፖለቲካ ባህሪ፣ በአሁኑ ወቅት በሀገሪቱ በሚካሄዱ ህዝባዊ ስብሰባዎችና ምርጫዎች ላይ ዋነኛ የስጋት ምንጭ እየሆነ መጥቷል።
ቅርብ ጊዜ በናይሮቢ የኦል ሴይንትስ ካቴድራል በተዘጋጀ የበጀት ስብሰባ ላይ በታጠቁ ወንዶች የተፈጸመው ጥቃት ለዚህ ማሳያ ተደርጎ ተወስዷል። ጥቃት አድራሾቹ በሲቪል ማህበረሰብ ቡድኖች አስተባባሪነት ይካሄድ የነበረውን ስብሰባ በመበተን፣ በርካታ አክቲቪስቶችን የደበደቡ ሲሆን ንብረትም ዘርፈዋል። የኬንያ የሀገር ውስጥ ጉዳይ ሚኒስትር ኪፕቹምባ ሙርኮመን እንደገለጹት፣ መርማሪዎች ጥቃቱን የፈጸሙትን አካላት ለይቶ ለማወቅ የክትትል ካሜራ (CCTV) ምስሎችን እያጠኑ ይገኛሉ።
ይህ በኬንያ የፖለቲካ ሂደት ውስጥ ዘላቂ ባህሪ እየሆነ የመጣው የወሮበላነት ተግባር፣ በ1990ዎቹ እና በ2000ዎቹ መጀመሪያ ላይ የነበሩትን «ዩዝ ፎር ካኑ 92» (YK’92)፣ «ካምጄሽ»፣ «ሙንጊኪ» እና «ታሊባን» የተባሉ ቡድኖችን ድርጊት የሚያስታውስ ነው። በአሁኑ ወቅት የሚንቀሳቀሱት ቡድኖች መደበኛ ቅርፅ የሌላቸውና ለመለየት አስቸጋሪ ቢሆኑም፣ በህዝባዊ ዝግጅቶች ላይ የሚፈጥሩት ሁከት ግን ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ መጥቷል።
ለምሳሌ በሰኔ 2025 (የ2024ቱን የታሪካዊ ተቃውሞ ለማሰብ በተዘጋጁ ሰልፎች ላይ) ከፖለቲካ ተዋናዮች ጋር ግንኙነት ያላቸው ቡድኖች በመሰግሰግ ከፍተኛ ጥቃትና ዘረፋ ፈጽመዋል። በጥቃቶቹ ላይ ስማቸው በተደጋጋሚ የሚነሳውና «ጋውቾ» በሚል ቅፅል ስም የሚታወቁት ካልቪንስ ኦኮት፣ ከክስተቱ በኋላ በናይሮቢ ትልቅ የመንግስት ሆስፒታል የቦርድ አባል ሆነው ተሹመዋል።
«ኦዲፖ ዴቭ» የተባለ ገለልተኛ የምርምር ቡድን ያወጣው ሪፖርት እንደሚያሳየው፣ ወሮበላነት አሁን ላይ የበለፀገ ቢዝነስ ሆኗል። ወጣቶች ተቃዋሚዎችን ለማስፈራራት ወይም የሰልፈኛ ቁጥርን ለማሳደግ እንደ ቀጣሪው የፖለቲካ ደረጃ ከ500 እስከ 1,500 የኬንያ ሺሊንግ (ከ3.80 እስከ 11.50 የአሜሪካ ዶላር) ይከፈላቸዋል። ይሁን እንጂ ድርጊቱ ለተቀጣሪዎቹ ወጣቶችም ከፍተኛ አደጋ አለው። ብዙዎቹ በቁጥጥር ስር በሚውሉበት ወቅት ቀጣሪዎቻቸው የዋስትና ገንዘብ ከመክፈልና ከማገዝ እንደሚቆጠቡ ታውቋል።
የኬንያ ቀጣሪዎች ፌዴሬሽን ባወጣው መረጃ መሰረት፣ በሀገሪቱ ከ10 ወጣቶች መካከል ሰባቱ (70%) ስራ አጥ ናቸው። ኬንያ ከ14 ወራት በኋላ ለምታካሂደው አጠቃላይ ምርጫ በምትዘጋጅበት በዚህ ወቅት፣ ይህ ከፍተኛ የስራ አጥነት መጠን ፖለቲከኞች በቀላሉ ተከፋይ ወሮበሎችን እንዲያገኙ ምቹ ሁኔታ እየፈጠረ መሆኑን ታዛቢዎች ያስጠነቅቃሉ።