የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ታሪካዊውን 76ኛ ዙር የምረቃ በዓል ዛሬ ባካሄደበት ወቅት የትምህርት ሚኒስትሩ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ በተገኙበት በደመቀ ሁኔታ አክብሯል። በዕለቱ የተገኙት ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ ለተመራቂዎች፣ ለአካዳሚክ ማህበረሰቡና ጥሪ ለተደረገላቸው እንግዶች ባደረጉት ታሪካዊ ንግግር፣ አዲሱ የትምህርት ሪፎርም የሀገሪቱን መዋቅራዊ ስብራት ለመጠገንና የሞራል ቀውስን ለመለወጥ የተጀመረ ወሳኝ እርምጃ መሆኑን በጥልቀት አብራርተዋል።
ሚኒስትሩ ንግግራቸውን የጀመሩት ዕለቱ በኢትዮጵያ የትምህርት ታሪክ ውስጥ አዲስ ምዕራፍ የተበሰረበት ታላቅ ዕለት መሆኑን በመግለጽ ነው። አዲሱ የትምህርት ሪፎርም ከተጀመረ በኋላ የተመረቁት እነዚህ የመጀመሪያዎቹ ተመራቂዎች፣ በብቃታቸውና በራሳቸው ልፋት ውጤት እዚህ በመድረሳቸው ስኬታቸው እጅግ የላቀ መሆኑን አብራርተዋል።
ፕሮፌሰር ብርሃኑ በንግግራቸው ወቅት እንደ ቻይና እና ደቡብ ኮሪያ ያሉ ሀገራት ከከፋ ድህነት ወጥተው ለአሁኑ የኢኮኖሚና የቴክኖሎጂ ልዕልና የብቃት ደረጃ ላይ የደረሱት በትምህርት ዘርፍ ላይ በወሰዱት ቁርጠኛ የሪፎርም እርምጃ መሆኑን አስገንዝበዋል። ደቡብ ኮሪያ ከጦርነት በኋላ ምንም አይነት የተፈጥሮ ሃብት ሳይኖራት፣ ብቸኛውና ዋነኛው ሀብት "የሰው አእምሮ" መሆኑን በመረዳት የትምህርት ባጀቷን በማሳደግና የፊደል መቁጠር ምጣኔን በአጭር ጊዜ 100% በማድረስ ለአለም ግዙፍ የቴክኖሎጂ ተቋማት ባለቤት መሆን መቻሏን ጠቅሰዋል። "አንድን ሀገር ከድህነት አረንቋ አውጥቶ ወደ እድገት ማማ መውሰድ የሚቻለው በተፈጥሮ ሃብት መብዛት ሳይሆን፣ ጥራት ያለውና ፍትሃዊ የትምህርት ስርአት መገንባት ሲቻል ብቻ ነው" ሲሉ ሚኒስትሩ አስገንዝበዋል።
ኢትዮጵያ ባለፉት አምስት አስርት አመታት በትምህርት ስርአቱ ላይ የገጠሙትን መዋቅራዊ ችግሮች ፊት ለፊት መጋፈጥ እንዳለባት ፕሮፌሰር ብርሃኑ አሳስበዋል። የፖለቲካ ስርአቶች ትምህርትን የርዕዮተ-አለም መቅረጫ ማድረጋቸው ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት "በነጻነት ማሰብ" እንዳይችሉ ማድረጉንና ይህም የትውልዱን የሞራል መሰረት በመናቅ ለሙስናና ለአድሏዊ አሰራር መስፋፋት ሰፊ አስተዋጽኦ ማድረጉን በግልጽ ተችተዋል።
ይህንን ስብራት ለመጠገን መንግስት በርካታ የሪፎርም ስራዎችን መጀመሩን የገለጹት ሚኒስትሩ፣ ከነዚህም መካከል በብቃት ላይ የተመሰረተና ሀገር በቀል እውቀትን ያካተተ አዲስ ስርአተ-ትምህርት መቀረጹን፣ ከ30 በላይ አዳዲስ የቅድመ-አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ተገንብተው ከአራት ሚሊዮን በላይ ህጻናት የትምህርት እድል ማግኘታቸውን ጠቅሰዋል። በተጨማሪም የ12ኛ ክፍል ሀገር አቀፍ ፈተና በዩኒቨርሲቲዎች ውስጥ እንዲሰጥ በማድረግ ኩረጃንና ስርቆትን በከፍተኛ ደረጃ መቀነስ መቻሉንና በማጥናት ብቻ ውጤት እንደሚገኝ በሁሉም ዘንድ መተማመን መፈጠሩን በኩራት ገልጸዋል።
ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የአካዳሚክና አስተዳደራዊ ነጻነት እንዲኖራቸው እየተሰራ መሆኑን የገለጹት ፕሮፌሰር ብርሃኑ፣ በዚህ ሂደት የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የመጀመሪያው ራስ-ገዝ (Autonomy) ዩኒቨርሲቲ ሆኖ መደራጀቱን ይፋ አድርገዋል። በቀጣዩ አመትም ሌሎች ዘጠኝ ተጨማሪ ዩኒቨርሲቲዎች የራስ-ገዝ ሂደታቸውን ለመጀመር ዝግጅታቸውን ማጠናቀቃቸውን ጠቁመዋል። የዩኒቨርሲቲ አመራር ምደባ ከዘር፣ ከመንደርና ከፖለቲካ ተጽዕኖ ሙሉ በሙሉ የጸዳ ሆኖ በእውቀትና በብቃት ላይ ብቻ የተመሰረተ እንዲሆን በቁርጠኝነት እየተሰራ መሆኑንም አረጋግጠዋል።
በመጨረሻም ሚኒስትሩ ለተመራቂ ተማሪዎች የስራውን አለም ሲቀላቀሉ ከሙስናና መሰል አድሏዊ አሰራሮች የጸዱ፣ ፍጹም ሀገራዊ ፍቅርና ህሊና ያላቸው፣ እና ሁሉንም ኢትዮጵያዊ እኩል እንደ ወገናቸው የሚያዩ ታማኝ አገልጋዮች እንዲሆኑ አደራ ብለዋል። ለተመራቂዎች ውጤት ማማር ሌት ተቀን ለደከሙ መምህራንና ወላጆችም ታላቅ አክብሮትና ምስጋናቸውን በማቅረብ ንግግራቸውን አጠቃለዋል።
አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ለ76ኛ ዙር በመጀመሪያ፣ በሁለተኛና፣ በሦስተኛ ዲግሪ እንዲሁም በሌሎች መርሃ ግብሮች ያስተማራቸውን 6 ሺህ 417 ተማሪዎች አስመርቋል።