አምዶች

Logo ከይር ታይምስ

የዲጂታል ዜና እምብርት

የቅርብ ዜና
ዜና / የሀገር ውስጥ ዜና

ኢትዮጵያ ዓለም አቀፉ የዕዳ መልሶ ማዋቀሪያ ሥርዓት በአስቸኳይ እንዲሻሻል ጠየቀች

በማስረሻ ቢተው | May 16, 2026

በማደግ ላይ ያሉ አገራትን ተጨባጭ የኢኮኖሚ ሁኔታ ከግምት ውስጥ ያላስገቡ የዓለም አቀፍ የፋይናንስ እና የንግድ ሥርዓቶች በአስቸኳይ መዋቅራዊ ማሻሻያ ሊደረግባቸው እንደሚገባ ኢትዮጵያ ጥሪ አቀረበች።

ሀገሪቱ ይህንን ጥሪ ያደረገችው በሕንድ ኒውደልሂ በተካሄደው የብሪክስ (BRICS) አገራት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች ስብሰባ ላይ መሆኑን ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የተገኘው መረጃ ያመለክታል።

በስብሰባው ላይ የተሳተፈው የኢትዮጵያ ልዑካን ቡድን እንደገለጸው፣ የወቅቱ ዓለም አቀፍ የዕዳ አያያዝ እና የንግድ መስፈርቶች ታዳጊ አገሮች ከኢኮኖሚ ጫና በፍጥነት እንዳያገግሙ ማነቆ እየሆኑባቸው ይገኛል።

ኢትዮጵያ ከረጅም የድርድር ሂደት በኋላ የውጭ ዕዳዋ በቡድን 20 (G20) የጋራ ማዕቀፍ (Common Framework) ሥር እንደገና እንዲዋቀርላት ባለፈው ዓመት መስማማቷ ይታወሳል። ይሁን እንጂ ይህ ማዕቀፍ ከተቀመጠለት ፍጥነት እና ዓላማ አንጻር አሁንም ሰፊ ቢሮክራሲያዊ ግትርነት የሚታይበት በመሆኑ ሂደቱ መዘግየቱ ተገልጿል።

እስከ አሁን ባለው ሂደት ከአበዳሪ አገራት መካከል የኢትዮጵያን ዕዳ መልሰው ለማዋቀር በተናጥል ከመንግሥት ጋር የመጨረሻ ስምምነት ላይ የደረሱት ፈረንሳይ እና ጣሊያን ብቻ መሆናቸው ተመልክቷል።

ይህም አሠራር በተለይ ታዳጊ ሀገራት በከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ እጥረት እና በዋጋ ግሽበት ውስጥ በሚገኙበት ወቅት፣ የኢኮኖሚ ማገገሚያ ዕድሎችን ሊያስተጓጉል እንደሚችል የኢኮኖሚ ባለሙያዎች ይስማማሉ። 

የኢትዮጵያ ልዑክ በኒውደልሂ ያቀረበው ጥሪም ይህ አድካሚና ዘገምተኛ ሥርዓት ተሻሽሎ ፈጣን ምላሽ የሚሰጥበት አቅጣጫ እንዲቀየስ የታለመ ነው።

የታሪክ እና የኢኮኖሚ ተንታኞች እንደሚጠቁሙት፣ ኢትዮጵያ ይህንን ጥሪ በብሪክስ (BRICS) መድረክ ላይ ማቅረቧ ዲፕሎማሲያዊ እና ስልታዊ ፋይዳው ከፍተኛ ነው። ሀገሪቱ የአባልነት ሚናዋን በመጠቀም፣ በምዕራባውያን ተቋማት ላይ ያላትን የፖሊሲ ቅሬታዎች እና የታዳጊ ሀገራትን የጋራ ድምፅ ይበልጥ ተደራሽ በሆነ መንገድ ለማስተጋባት ምቹ ሁኔታ ፈጥሮላታል።

ይሁን እንጂ፣ ከምዕራባውያን የዕዳ ጫና እና መዋቅራዊ ቅድመ-ሁኔታዎች ለመሸሽ በሚደረገው ጥረት፣ የብሪክስ አባል ወደሆኑትና እንደ ቻይና ያሉ ግዙፍ ምሥራቃውያን አበዳሪዎች ዘንድ የሚኖረው የዕዳ ትስስር በጥንቃቄ ሊመራ እንደሚገባው ተመልክቷል።

የኢትዮጵያ የፖሊሲ ወቀሳ በዕዳ ማዋቀሩ ላይ ብቻ የተገደበ አይደለም። ሀገሪቱ የዓለም ንግድ ድርጅትን (WTO) ለመቀላቀል ረጅም ዓመታትን የፈጀ ድርድር እያደረገች የምትገኝ ሲሆን፣ ድርጅቱን ለመቀላቀል የተቀመጡ መስፈርቶች የታዳጊ አገራትን ተጨባጭ አቅም ያገናዘቡ እንዲሆኑ በስብሰባው ላይ ጠይቃለች።

የንግድ ድርጅቱ የሚያስቀምጣቸው ጥብቅ መስፈርቶች፣ የሀገር ውስጥ ታዳጊ ኢንዱስትሪዎችን እና አምራቾችን የመወዳደር አቅም አደጋ ላይ እንዳይጥሉ ስጋት ስላለ፣ የገበያ በሯን በይፋ ከመክፈቷ በፊት የደረጃ ማሻሻያ እንዲደረግላት መጠየቋ ተገቢ እና ስልታዊ አካሄድ መሆኑ ተገልጿል።

በኒውደልሂ የተሰማው የኢትዮጵያ ድምፅ በዓለም አቀፍ መድረክ ተደማጭነት እንዲኖረው፣ ሀገሪቱ ከውጭ ትችቶች ባሻገር የውስጥ የኢኮኖሚ መዋቅሯን ማጠናከር እንዳለባት ባለሙያዎች ያሳስባሉ።

ዓለም አቀፉን ሥርዓት መውቀስ እንደተጠበቀ ሆኖ፣ የተወሰዱ የውጭ ዕዳዎችን ይበልጥ ምርታማ በሆኑ፣ የወጪ ንግድን በሚያሳድጉ እና የሀገር ውስጥ አቅምን በሚገነቡ ዘላቂ ፕሮጀክቶች ላይ ማዋል የመንግሥት ቀዳሚ የቤት ሥራ ሊሆን እንደሚገባ ተመልክቷል።

Recommended
Bottom Advertisement
Learn More

ተጨማሪ ዜናዎችን ያንብቡ

ማህበራዊ - ሚዲያ

የከይር ታይምስ ዘገባዎችን በሁሉም ማህበራዊ ሚዲያ አማራጮች ይከታተሉ