የኢራኑ ፕሬዝዳንት መሱድ ፔዜሽኪያን በኳታር ከታገደባቸው 12 ቢሊዮን የአሜሪካ ዶላር አጠቃላይ ሀብት ውስጥ ስድስት ቢሊዮን ዶላሩ ሊለቀቅላቸውና ወደ ሀገሪቱ ሊመለስ መሆኑን አስታወቁ። ይህ ይፋዊ መግለጫ የተሰማው በፓኪስታን እና በኳታር አደራዳሪነት በአሜሪካ እና በኢራን መካከል ለተደረገው እንዲሁም አራት ወራት የዘለቀውን የሁለቱ ሀገራት ቀጥተኛ ጦርነትና ቀውስ ለማቆም የሚያስችለውን የመግባቢያ ስምምነት ተከትሎ ነው።
ፕሬዝዳንት ፔዜሽኪያን በቅድስት ከተማ ቁም ከከፍተኛ የሃይማኖት መሪዎች ጋር ባደረጉት ስብሰባ ላይ እንደገለጹት፥ የተለቀቀው ይኸው ስድስት ቢሊዮን ዶላር በኳታር ከሚገኘው የኢራን ይዞታ ውስጥ ግማሽ ያህሉን የሚሸፍን ሲሆን፣ ቀሪውን ግማሽ ፈንድ ለማስለቀቅም መንግሥታቸው አስፈላጊውን ክትትል እያደረገ ይገኛል። ፕሬዝዳንቱ ይህንን ዲፕሎማሲያዊ ስኬት "ለኢራን ሕዝብ ታላቅ ድል" በማለት የገለጹት ሲሆን፣ በሀገሪቱ የነዳጅ እና የፔትሮኬሚካል ምርቶች የወጪ ንግድ ላይ ተጥለው የነበሩ ማዕቀቦች መነሳታቸውንም ይፋ አድርገዋል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ፣ በሁለቱ ወገኖች መካከል የተደረሰው የመግባቢያ ስምምነት (MoU) በባሕረ ሰላጤው አካባቢ የነበረውን ከፍተኛ ወታደራዊ ውጥረት ለማርገብና በዓለም አቀፍ የንግድ መስመር በሆነው በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ የነበረውን የጋራ ጥቃት ለማቆም ያለመ ነው። በስምምነቱ መሠረት ሁለቱ ሀገራት በ60 ቀናት ውስጥ ዘላቂና የመጨረሻ ሰላም ላይ ለመድረስ ድርድር የሚያደርጉ ሲሆን፣ ለዚህም የኢራን እና የአሜሪካ የቴክኒክ ቡድኖች በዶሃ (ኳታር) ተገናኝተው ዝርዝር ጉዳዮች ላይ እንደሚመክሩ ዲፕሎማሲያዊ ምንጮች ጠቁመዋል።
ምንም እንኳን በቅርብ ቀናት ውስጥ የተከሰቱ ወታደራዊ ግጭቶች እና ቀጣናዊ ውጥረቶች በሂደቱ ላይ ተግዳሮት ቢፈጥሩም፣ አደራዳሪ አካላት ስምምነቱ እንዳይደናቀፍ በስተጀርባ ሰፊ የዲፕሎማሲ ጥረት እያደረጉ ይገኛሉ። ፕሬዝዳንት ፔዜሽኪያን አሜሪካ በኢኮኖሚና በመሠረተ ልማት ጥቃቶች ኢራንን ለማዳከም ያደረገችው ሙከራ መክሸፉን ጠቅሰው፣ ሀገራቸው የኑክሌር መሣሪያ የመታጠቅ ፍላጎት እንደሌላትና የኑክሌር መርሃ ግብሯን ለሀገራዊ ፍላጎትና ለሰላማዊ ዓላማ ብቻ እንደምታውለው በድጋሚ አረጋግጠዋል።
ይህ የገንዘብ ልቀት በሀገሪቱ ላይ የተጣሉትን የኢኮኖሚ ማዕቀቦች ጫና በከፍተኛ ሁኔታ የሚቀንስ በመሆኑ፣ የቴህራን መንግሥት የተለቀቀውን ሀብት የሕዝቡን ማኅበራዊ ድጋፍ ለማስፋፋትና የወደሙ መሠረተ ልማቶችን መልሶ ለመገንባት እንደሚጠቀምበት ተገልጿል። የተፈረመው የመግባቢያ ስምምነት ሙሉ በሙሉ ተግባራዊ ሲሆን በሁለቱ ሀገራት መካከል ለረጅም ጊዜ የዘለቀውን የፖለቲካ ውጥረት በአዲስ ምዕራፍ ሊቀይረው እንደሚችል የዓለም አቀፍ ጉዳዮች ተንታኞች በመግለጽ ላይ ናቸው።