ዴንማርካዊው የቮልፍስበርግ እና የቀድሞ የማንችስተር ዩናይትድ አማካይ ክሪስቲያን ኤሪክሰን፣ ብሔራዊ ቡድኑ ከዩክሬን ጋር እያደረገው በነበረው የወዳጅነት ጨዋታ ላይ በድጋሚ እራሱን ስቶ መውደቁ ተሰማ። ክስተቱን ተከትሎም በኦዴንሴ ስታዲየም ሲደረግ የነበረው የሁለቱ ሀገራት ጨዋታ ሊቋረጥ ችሏል።
በኦዴንሴ በተደረገው በዚህ የወዳጅነት ጨዋታ ላይ የ34 ዓመቱ አማካይ ጨዋታው በተጀመረ በ65ኛው ደቂቃ ላይ ነበር በድንገት ሜዳ ላይ የወደቀው። በወቅቱ በስታዲየሙ የነበሩ የሁለቱም ቡድኖች ተጫዋቾች፣ የቴክኒክ ክፍሉ አባላት እና ደጋፊዎች ከፍተኛ ድንጋጤ ውስጥ ገብተው የነበረ ሲሆን፣ የሁለቱም ሀገራት ተጫዋቾች በኤሪክሰን ዙሪያ ክብ በመስራት የህክምና ባለሙያዎች አስፈላጊውን እርዳታ እንዲያደርጉለት ምቹ ሁኔታን ፈጥረዋል።
የዴንማርክ ብሔራዊ ቡድን ዋና ዶክተር ሞርተን ቦውሰን ከክስተቱ በኋላ ለሀገሪቱ መገናኛ ብዙሃን በሰጡት መግለጫ፣ ተጫዋቹ በአሁኑ ወቅት መንቃቱን እና በጥሩ የጤንነት ሁኔታ ላይ እንደሚገኝ አረጋግጠዋል። ዶክተሩ "ክሪስቲያን በጥሩ ሁኔታ ላይ ይገኛል፤ ከሜዳም በገዛ እግሩ ተራምዶ ወጥቷል" ብለዋል። አክለውም የልብ ምት ማስተካከያ መሣሪያው (ICD) እንደተጠበቀው በአግባቡ መሥራቱን ገልጸው፣ ተጫዋቹ ለአጭር ሰከንዶች እራሱን ስቶ የነበረ ቢሆንም በፍጥነት ሊነቃ እንደቻለና በአሁኑ ሰዓት ለተጨማሪ ምርመራ ወደ ሆስፒታል መወሰዱን አስታውቀዋል።
የዴንማርክ ብሔራዊ ቡድን አምበል ፒየር-ኤሚል ሆይብየር በበኩሉ፣ "ሁኔታው በጣም አስደንጋጭ ነበር። ነገር ግን ሁሉም ሰው ተጫዋቹን ለመርዳት በፍጥነት የተንቀሳቀሰበት መንገድ የሚደነቅ ነው" ሲል ስሜቱን ገልጿል። የቡድኑ አሰልጣኝ ብሪያን ሪመርም ቡድኑ በአሁኑ ሰዓት ከተጫዋቹ እና ከህክምና ባለሙያዎች ጋር የማያቋርጥ ግንኙነት እያደረገ መሆኑን ጠቁመዋል።
ክሪስቲያን ኤሪክሰን ከዚህ ቀደም በ2021 እ.ኤ.አ (በ2013 ዓ.ም) በተካሄደው የዩሮ 2020 ውድድር ላይ ከፊንላንድ ጋር በተደረገ ጨዋታ በተመሳሳይ የልብ ህመም (Cardiac Arrest) አጋጥሞት በሜዳ ላይ መውደቁ ይታወሳል። በወቅቱ በተደረገለት አስቸኳይ የህክምና እርዳታ ህይወቱ የተረፈ ሲሆን፣ በልቡ ላይ ICD (Implantable Cardioverter-Defibrillator) የተባለ የልብ ምት ማስተካከያ መሣሪያ ተገጥሞለት ከስምንት ወራት ማገገም በኋላ ወደ እግርኳስ መመለሱ ይታወሳል።
ተጫዋቹ ወደ ጨዋታ ከተመለሰ በኋላ ለብሬንትፎርድ እና ለማንችስተር ዩናይትድ የተጫወተ ሲሆን፣ ባለፈው የክረምት የዝውውር መስኮት ደግሞ የጀርመኑን ቮልፍስበርግ በመቀላቀል በውድድር ዓመቱ 34 ጨዋታዎችን ማድረግ ችሏል። ኤሪክሰን ትናንት እራሱን ስቶ በወደቀበት ወቅት ለሀገሩ ዴንማርክ 151ኛ ዓለም አቀፍ ጨዋታውን እያደረገ ነበር። ሆስፒታል የሚገኘው ኤሪክሰን ለቡድን አጋሮቹ በላከው መልዕክት "ደህና ነኝ" በማለት ሰላምታውን እንዳቀረበላቸው ተገልጿል።